• No results found

ጀብሃ እና ሻዕቢያ (2)

N/A
N/A
Protected

Academic year: 2021

Share "ጀብሃ እና ሻዕቢያ (2)"

Copied!
55
0
0

Loading.... (view fulltext now)

Full text

(1)

(1961-1991 G.C)

Click to buy NOW!

PDF-XChange w w w .tr acker-softwar e.c

om Click to buy NOW!

PDF-XChange w w w .tr acker-softwar e.c om

(2)

ጀብሃ እና ሻዕቢያ (1961-1991 G.C) --- ጸሓፊ፡ አፈንዲ ሙተቂ --- ብዙ አንባቢዎች በፌስቡክ እና በኢ-ሜይል ከሚያቀርቡልኝ ጥያቄዎች መካከል አንዱ የኤርትራ የፖለቲካ ድርጅቶችን የሚመለከተው ነው፡፡ ጥያቄው ንባብ የሚያሻው በመሆኑ ለተወሰነ ጊዜ ወደ ጎን ስገፋው ኖሬአለሁ፡፡ በዚህ ሰሞን የአምባሳደር ዘውዴ ረታን “የኤርትራ ጉዳይ”፣ የፖል ሄንዝን Eritrea’s War እና የጌታቸው ሀይሉን “ቀያይ ተራሮች” በድጋሚ ካነበብኳቸው በኋላ ግን የጓደኞቼን ጥያቄ ለመመለስ ተነሳሳሁ፡፡ እናም “ጀብሃ” እና “ሻዕቢያ”ን በመጠኑ የሚያስቃኘውን ይህንን ጽሑፍ እንዲህ አሰናድቼዋለሁ (በጽሑፉ ውስጥ ያለው የዘመን አቆጣጠር በሙሉ በአውሮፓዊያን ካሌንደር ነው የተጠቀሰው)፡፡ ቅድመ-ታሪክ እ.ኤ.አ በ1952 ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር በፌዴሬሽን ተሳሰረች፡፡ ይህ የፌዴሬሽን አሰራር ከመነሻው ላይ የብዙሃኑ ኤርትራዊ ድጋፍ አግኝቶ ነበር፡፡ ወደ ተግባር ሲተረጎም ግን ብዙዎች ግራ መጋባት ጀመሩ፡፡ ኤርትራዊያኑ አስተዳደራቸው ሙሉ በሙሉ ነጻ ሆኖ በስም ብቻ ከሃይለ ስላሴዋ ኢትዮጵያ ጋር የተሳሰረ ነበር የመሰላቸው፡፡ በትክክለኛው አገላለጽ ግን ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር የተያያዘችው እንደ ነጻ ሀገር ሳይሆን እንደ አንድ ራስ ገዝ ክፍለ ሀገር በመሆን ነበር፡፡ የኤርትራ መንግሥት ተብሎ የተሰየመው አካል በውስጥ ጉዳዮች ላይ በነጻነት የመወሰን መብት ቢሰጠውም በውጪ ጉዳይ፣ በመከላከያ፣ በፋይናንስ፣ በወደቦችና በመገናኛ ዘርፎች የመወሰን ስልጣን አልነበረውም፡፡ እነዚህ ጉዳዮች የሚከናወኑት በፌዴሬሽኑ ህገ-መንግሥት መሰረት የፌዴራሉ መንግስት ሆኖ እንዲሰራ ስልጣን በተሰጠው የአጼ ሀይለ ስላሴ ንጉሣዊ አስተዳደር ነው፡፡ ኤርትራዊያኑም እንደ ኢትዮጵያ ዜጋ ነበር የሚቆጠሩት፡፡ በዚህም የተነሳ አንዳንድ ኤርትራዊያን ከፌዴሽኑ ምስረታ በኋላ “እንግሊዝና አሜሪካ ለሀይለስላሴ መንግሥት ሸጡን” የሚል ተቃውሞ ማሰማት ጀምረው ነበር፡፡ በዚያ ዘመን የተቃውሞው መሪ ሆነው የወጡት አቶ ወልደአብ ወልደማሪያም የሚባሉት የቀድሞው “ሊበራል ፕሮግሲቭ ፓርቲ” መሪ እና “የራቢጣ አል-ኢስላሚያ ፓርቲ” መሪ የነበሩት ሱልጣን ኢብራሂም ናቸው፡፡ እንደዚያም ሆኖ ግን ፌዴሬሽኑ ለሶስት ዓመታት ያህል በነጻነት ቆየ፡፡ ከኤርትራ ህዝብ የሚበዛው ክፍል በፌዴሬሽኑ መንግስት ደጋፊነት ኖረ፡፡ የመጀመሪያው የኤርትራ ስራ አስፈጻሚ (Chief Executive) የነበሩት ደጃዝማች ተድላ ባይሩ በ1955 ስልጣናቸውን በፈቃዳቸው ሲለቁ ግን ኤርትራ የተቃውሞ መድረክ መሆን ጀመረች፡፡ በተለይ የአጼ ኃይለ ስላሤ የቅርብ ሰው የሆኑት የቢትወደድ አስፍሐ ወልደሚካኤል የኤርትራ ስራ አስፈጻሚ ሆኖ መመረጥ ከፍተኛ የህዝብ ተቃውሞ አስነሳ፡፡ በ1956 የፖለቲካ ፓርቲዎችና ነጻ ፕሬስ ሲታገዱ አብዛኛው ኤርትራዊ የፌዴሬሽኑ መጥፊያ የተቃረበ መሆኑን መተንበይ ጀመረ፡፡ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትዋሃድ የደከሙ ሰዎች እየተገፉ ሌሎች መሾማቸው ደግሞ ነገሩን አባባሰው፡፡ እነዚህ የአንድነት ወገን የሚባሉ መሪዎች “ባይተዋር ሆነናል” በማለት ለአጼ ሀይለ ስላሴ አቤቱታ አቀረቡ፡፡ ፌዴሬሽኑን የመጠበቅ ግዴታ የተሰጠው የአጼ ኃይለ ስላሴ መንግሥት ግን የፌዴሬሽኑን ህልውና የሚያናጉ

(3)

እርምጃዎች ሲወሰዱ አይቶ እንዳላየ ሆኖ አለፈ፡፡ በተለይ ኤርትራን ከኢትዮጵያ ጋር ለማዋሃድ በእጅጉ የደከሙት የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተ ወልድ ፌዴሬሽኑ እንዳይፈርስ የሚቻለውን ሁሉ ቢያደርጉም አጼ ኃይለስላሴ በተቃራኒው የቢትወደድ አስፋሐ “አይዞህ ባይ” ሆኑ፡፡ የቢትወደድ አስፋሐ መንግሥት የሚወስደው እርምጃ እለት ተዕለት እየጠነከረ ሄደ፡፡ በ1958 የኤርትራ ሰራተኞች ኮንፌዴሬሽን የጠራው የስራ ማቆም አድማ በሀይል ተደመሰሰ፡፡ ብዙ ሰዎች ተገደሉ፡፡ በዚህም የተነሳ በርካታ ኤርትራዊያን “ሓርነት” የሚል ድምጽ ማሰማት ጀመሩ፡፡ ሆኖም የቢትወደድ አስፋሐ መንግሥት የህዝቡን ተቃውሞ ከምንም አልቆጠረውም፡፡ በ1958 የፌዴሬሽኑ የስራ ቋንቋዎች የሆኑት ትግርኛና ዐረብኛ ታግደው በአማርኛ ተተኩ፡፡ በ1959. የኤርትራ ሰንደቅ ዓላማ ታገደ፡፡ በ1962 ዓ.ል. ፌዴሬሽኑ ፈርሶ ኤርትራ የኢትዮጵያ ክፍለ ሀገር መሆኗ ታወጀ፡፡ የኤርትራ ፌዴሬሽን የፈረሰበት ታሪካዊ ሂደት በአጭሩ ይህንን ይመስላል፡፡ ለሰላሳ ዓመታት የኢትዮጵያ ህዝቦችን ደም ሲያስገብር የነበረው ጦርነት የተለኮሰው ይህንን እርምጃ ተከትሎ ነው፡፡ ያኔ የተፈጸመው ብዙዎችን ያሳዝናል፤ ያስቆጫልም፡፡ በተለይ የሚያስቆጨው ግን የአጼ ሃይለ ስላሴ መንግሥት የመካሪዎቹን ጥቆማ አልቀበልም በማለት ሲፈጽማቸው በነበሩት ስህተቶች የተነሳ ኢትዮጵያ የባህር በር እንድታጣ ለማድረግ መብቃቱ ነው፡፡ ኤርትራን ከኢትዮጵያ ጋር በፌዴሬሽን ለማዋሃድ የደከሙት ጸሓፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ ለንጉሳቸው ሲሰጡት የነበረው ምክር በስራ ላይ ቢውል ኖሮ የዛሬው ሁኔታ ሌላ መልክ በያዘ ነበር (ምናልባትም እኔ ራሴ ይህንን ጽሑፍ ባልጻፍኩ ነበር)፡፡ የቢትወደድ አስፋሐ እርምጃ በተጠናከረበት በ1956 ገደማ አንዳንድ ኤርትራዊያን “ፌዴሬሽኑ የፈረሰ እንደሆን ምን እናድርግ” እያሉ በድብቅ የሚወያዩበትን “ማህበር ሸውአተ” የተሰኘ እድር መሳይ ማህበር መስርተው ነበር፡፡ ይህ ማህበር በጅምሩ ላይ ዝግ ብሎ ይጓዝ ነበር፡፡ በ1959 የኤርትራ ባንዲራ ሲሰረዝ ግን “የፌዴሬሽኑ መፍረስ እውን ነው” በማለት ደመደመ፡፡ በዚህም የተነሳ የማህበሩ መስራቾች እንቅስቃሴአቸው ድርጅታዊ መልክ እንዲይዝ አደረጉት፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላም ከዚሁ ማህበር አስኳል “ምንቕስቓስ ሓርነት ኤርትራ”/Eritrean Liberation Movement ወይንም በአጭሩ “ሀረካ” በሚል ስያሜ የሚጠራ የፖለቲካ ድርጅት ተወለደ (“ሀረካ” በዐረብኛ “እንቅስቃሴ” ወይም “ንቅናቄ” ማለት ነው፤ ድርጅቱ በሙሉ የዐረብኛ ስሙ “ሀረካት ታህሪረል ኤሪትሪያ” ይባላል፤ “የኤርትራ ነጻነት ንቅናቄ” ማለት ነው)፡፡ “ሀረካ” ሁለት አማራጮችን ይዞ ነው ወደ ትግሉ የገባው፡፡ ቀዳሚ ምርጫው “የኤርትራ ፌዴሬሽን መፍረስ የለበትም” የሚል ሲሆን ዓላማውም የቢትወደድ አስፋሐ እና የአጼ ኃይለ ስላሴ መንግሥት ሹማምንት የፌዴሬሽኑን አሰራር በትክክል በስራ ላይ እንዲያውሉ መጠየቅ ነው፡፡ ሁለተኛው አማራጭ “ኤርትራ ራሷን የቻለች ሉዓላዊት ሀገር ሆና ነጻ ትውጣ” የሚል ነው፡፡ ሆኖም የ“ሀረካ” ቀዳሚ ምርጫ ፌዴሬሽን እንጂ “ነጻነት” አልነበረም፡፡ የሀረካ መሪዎች ጥያቄአቸውን ለኤርትራ አስተዳደር አቀረቡ፡፡ ይሁንና የቢትወደድ አስፋሐ መንግሥት በጎ ምላሽ ነፈጋቸው፡፡ እንዲያውም “የዐረብ ምንደኛ” እና “ሽብር ፈጣሪ” በማለት ከሰሳቸው፡፡ በዚህም የተነሳ ሀረካዎች ለትጥቅ አመጽ ተነሳሱ፡፡ በፌዴሬሽኑ ማክተሚያ ዋዜማ ላይ

(4)

ንቅናቄው 50 ያህል ተዋጊዎችን አደራጅቶ ወደ ሳህል በረሃ ወረደ፡፡ ሆኖም ለሶስት ዓመታት ያህል

የሚረባ እንቅስቃሴ ሳያደርግ ከርሱ በኋላ በተቋቋመ አዲስ ድርጅት ተበለጠ፡፡ በ1964 ገደማም

አዲሱ ድርጅት በከፈተበት ጥቃት ክፉኛ ተመታ፡፡ የሀረካ ህልውናም በዚያው አከተመ፡፡

ጀብሃበኤርትራሜዳ

አዲሱ ድርጅት “ተጋድሎ ሐርነት ኤርትራ/Eritrean Liberations Front ይባላል፡፡ የታሪክ

ሰነዶችና መላው ኤርትራዊያን ድርጅቱን የሚጠሩት ግን “ጀብሃ” በሚል አጭር ስም ነው፡፡ “ጀብሃ” የሚለው ቃል “ጀብሃት ታሕሪረል ኤሪቲሪያ” ከሚለው የድርጅቱ የዐረብኛ መጠሪያ ተቀንጭቦ የወጣ ነው፡፡ ይህም ድርጅቱን ከ“ሀረካ” ለይቶ ለመጥራት በሚደረግ ጥረት የተፈጠረ ልማድ ነው (የሁለቱ ድርጅቶች የዐረብኛ መጠሪያ አንድ ዓይነት ሆኖ በስሞቹ መጀመሪያ ላይ ባሉት “ጀብሃ” እና “ሀረካ” በሚሉት ቅጽሎች ብቻ ነው የሚለዩት)፡፡ “ተሓኤ”/ጀብሃ የተመሰረተው በ1961 በካይሮ ከተማ ነው፡፡ የድርጅቱ መስራቾች በስደት ላይ የነበሩ ኤርትራዊያን ተማሪዎች፣ የቀድሞ “ራቢጣ” እና “ፕሮግሬሲቭ ፓርቲ” አባላት፣ ከኤርትራ ፓርላማ የኮበለሉ ጥቂት ግለሰቦችና በዐረቡ ዓለም የሚኖሩ ነጋዴዎች ነበሩ፡፡ ድርጅቱ በምስረታ ጉባኤው ከኤርትራ ነጻነት በስተቀር ሌሎች አማራጮችን እንደማይቀበል አስታወቀ፡፡ ፌዴሬሽን የሚባለው አስተሳሰር ለኤርትራዊያን በጭራሽ የማያስፈልግ የባርነት እስር ቤት ነው በማለት ደመደመ፡፡ ከኢትዮጵያ መንግሥትም ጋር በነጻነት ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር በሌሎች አጀንዳዎች እንደማይደራደር ገለጸ፡፡ የኤርትራ ፓርላማ ፕሬዚዳንት የነበረውን ኢድሪስ መሐመድን በሊቀመንበርነት መረጠ፡፡ ጀብሃ በምስረታው ማግስት ለትጥቅ አመጽ መዘጋጀት ጀመረ፡፡ በሀገር ቤት ካሉ ባላባቶች ጋር ግንኙነት ከተፈጠረ በኋላ ምዕራባዊው የኤርትራ ቆላ ለትግል ምቹ መሆኑን አመነበት፡፡ የአካባቢው ታዋቂ ባላባት የሆኑት “ሃሚድ ኢድሪስ አዋቴ” የሚባሉት የቤኒ አምር ጎሳ ተወላጅ የግንባሩን የትጥቅ ትግል እንዲመሩ ውክልና ተሰጣቸው፡፡ በኝህ ሰው አስተባባሪነትም አስራ አንድ ሰዎችን ያቀፈ አንድ ቡድን መስከረም 1/1961 በኤርትራ ምድር ለ30 ዓመታት የሚቆየውን የትጥቅ ትግል በምዕራባዊው የባርካ አውራጃ ጀመረ (ሆኖም ሃሚድ አዋቴ ከአንድ ዓመት በኋላ በተደረገ ውጊያ ላይ ተገድለዋል)፡፡ ጀብሃ ወደ ትግሉ ሜዳ የገባው በከረረ ስሜት ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጸው ከኤርትራ ነጻነት በስተቀር በየትኛውም አማራጭ ላይ ለመደራደር ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ የትግል ዓላማው ኤርትራን ነጻ ሀገር ማድረግ ከመሆኑ በመለስ ድርጅቱ በምስረታው ዋዜማ የየትኛው የርዕዮተ-ዓለም አቅጣጫ ተከታይ እንደነበረ በትክክል ለመረዳት ይቸግራል፡፡ በርካታ ጸሓፊያን “ተሓኤ” (ጀብሃ) ብሄርተኛ ከመሆኑ ውጪ የተለየ ጎራ ተከታይ እንዳልነበረ ያስረዳሉ፡፡ አንዳንዶች ግን ድርጅቱ ከኢራቅና ከሶሪያ “በዕሥ” (“Ba’th” ) ፓርቲዎች ጋር የነበረውን ጠንካራ ግንኙነት በመመልከት “ጀብሃ የዐረብ ሶሻሊዝም ፍልስፍና ተከታይ ነበር” ይላሉ፡፡ በርግጥም “ጀብሃ” በዐረቦች ዘንድ ከፍተኛ እውቅናና ድጋፍ አግኝቶ ነበር፡፡ ራሱንም እንደ ዐረብ ብሔርተኛ ድርጅት የማየት አዝማሚያዎች ነበሩት፡፡ ሆኖም ይህንን ሁሉ ለታክቲክ ሲባል የሚያደርገው ነው የሚመስለው፡፡ ድርጅቱ ዐረባዊ እየመሰለ እና ዐረብኛን የስራ ቋንቋነት በማድረግ

(5)

እየተገለገበት እንኳ ዐረብ ካልሆኑ የኮሚኒስት ሀገራትም ጋር ግንኙነት ነበረው፡፡ ለምሳሌ ጀብሃ ከኩባ፣ ቻይና እና ሶቪየት ህብረት ከፍተኛ ድጋፍ አግኝቶ ነበር፡፡ እንዲሁም የሶሻሊዝም ጠላት ናቸው ከሚባሉት ሳዑዲ ዐረቢያን ከመሳሰሉ ሀገራት ጋር የነበረው ግንኙነት በጣም የጠነከረ ነው፡፡ ጣሊያንን የመሳሰሉ የምዕራብ ሀገራትም የድርጅቱ ደጋፊዎች ነበሩ፡፡ ከዚህ ሁሉ እንደምንረዳው ድርጅቱ የታክቲክ ወዳጅ እንጂ የርዕዮተ ዓለም ወዳጅ ነበረው ለማለት ይከብዳል፡፡ የጀብሃ መስራቾች በአብዛኛው የትግረ ቋንቋ ከሚናገሩት የቤኒአምር፣ አሳውርታ እና ቢለን ጎሳዎች የተውጣጡ ነበሩ፡፡ በዚህም የተነሳ በምስረታው ዘመን ከድርጅቱ አባላት ዘጠና በመቶ የሚሆኑት ሙስሊሞች ነበሩ፡፡ የድርጅቱ እንቅስቃሴም በቆላማዎቹ የሳህል፣ ከረን እና ባርካ አውራጃዎች የተገደበ ነበር፡፡ በምስረታው ዘመን ከሀምሳ የማይበልጡ ተዋጊዎች የነበረው ይህ እንቅስቃሴ ከሁለት ዓመታት በኋላ ሰራዊቱን በብዙ እጥፍ በማሳደግ ወደ ሶስት ሺህ አድርሶታል፡፡ በመጀመሪያዎቹ ዓመታት የአጼ ሀይለስላሴ መንግስት ጀብሃን እንደ ተራ የሽፍታ ስብስብ ስለቆጠረው በፖሊስ ሀይል አሳድዶ ሊያጠፋው ሞክሮ ነበር፡፡ በ1963 ከከረን ከተማ ወጣ ብሎ በሚገኝ አንድ ስፍራ ላይ በተደረገ ከባድ ውጊያ በርካታ ፖሊሶች ከሞቱ በኋላ ግን የንጉሡ መንግሥት መደበኛ ሰራዊቱን ወደ ኤርትራ ማንቀሳቀስ ግድ ሆኖበታል፡፡ ጀብሃ በምስረታው ማግስት ጥርት ያለ የድርጅት መዋቅር አልነበረውም፡፡ በ1964 ግን የድርጅቱን አመራር ማስተካከል አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ መዋቅሩን በልዩ ልዩ እርከኖች በመከፋፈል በስራ ላይ አውሎታል፡፡ በዚህም መሰረት አምስት አባላት ያሉት “ቃኢዳ አል-አማ” (በዐረብኛ “ጠቅላይ መምሪያ” እንደማለት ነው ) የሚባለው አካል የድርጅቱ ከፍተኛ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሆኖ ተሰየመ፡፡ የግንባሩን አጠቃላይ የፖሊሲ ውሳኔዎች የሚያስፈጽመው ይህ አካል ነው፡፡ ድርጅቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚወክለውም ይኸው “ቂያዳ አል-አማ” ነው፡፡ ኢድሪስ መሀመድ፣ ኡሥማን ሳልህ ሳቤ፣ ጣሃ መሐመድ ኑር፣ ኢድሪስ ገላውዴዎስ እና አብደላ ኢድሪስ የጀብሃ ስራ አስፈጻሚዎች ነበሩ፡፡ የስራ አስፈጻሚው ኮሚቴው የሚቀመጠው የድርጅቱ ዋና ጽ/ቤት ባለበት የካይሮ ከተማ ነው፡፡ ኢድሪስ መሐመድ እና ኢድሪስ ገላውዴዎስ የግንባሩ ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት፣ ዑስማን ሳልህ ሳቤ የድርጅቱ የውጪ ጉዳይ ሃላፊ ነበሩ፡፡ ከስራ አስፈጻሚው ኮሚቴው ዝቅ ብሎ ደግሞ “አብዮታዊ እዝ” የሚባል ምክር ቤት አለ፡፡ የዚህ እዝ ተቀማጭነቱ በሱዳኗ ከሰላ ከተማ ሲሆን መደበኛ ተግባሩም በአምስቱ ዞኖች የሚከናወኑትን ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ ተግባራት ማቀናበርና ማቀላጠፍ ነው (ስለዞን አወቃቀር ከታች እንመጣበታለን)፡፡ የመጀመሪያው የጀብሃ ወታደራዊ አዛዥ ዑመር ኢዛዝ ይባላል፡፡ ይህ ሰው የብሌን ብሄረሰብ ተወላጅ ሲሆን ጀብሃ እስከዛሬ ካፈራቸው አዋጊዎች በጀግንነቱ የሚወደሰው እርሱ ነው፡፡ ዑመር ኢዛዝ የተወለደው በከረን ከተማ ነው፡፡ በወጣትነቱ ወደ ሱዳን ተሰዶ በሱዳን ጦር ሀይል ውስጥ በመቀጠር እስከ ሻምበል ማዕረግ ለመያዝ ችሏል፡፡ ከርሱ ጋር የተዋጉና አሁንም በህይወት ያሉ የጀብሃ አባላትና መሪዎች በጣም ያደንቁታል፡፡ ሆኖም በጭካኔው ወደር እንዳልነበረው ታሪኩን የጻፉ ወገኖች ይመሰክራሉ (ዑመር ኢዛዝ በ1972 በውጊያ ላይ ሞቷል)፡፡ ጀብሃ እስከ 1965 ሲያካሄደው የነበረው ወታደራዊ ኦፕሬሽን በአንድ የዘመቻ ማዕከል ነበር የሚመራው፡፡ በነዚያ ዓመታት ግንባሩ ነጻ ያወጣው ትልቅ ከተማ ባይኖርም ሳህል እና ባርካ በሚባሉት ቆላማ የኤርትራ አውራጃዎች ውስጥ ያለው የገጠሩ ክፍል በቁጥጥሩ ስር ገብቶ ነበር፡፡ ከ1965 ጀምሮ የአጼ ኃይለ ስላሤ መንግሥት የግንባሩን እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር በሚል የወሰዳቸው የጅምላ ቅጣቶች ተቃራኒ ውጤቶች ነው የነበራቸው፡፡ በተለይ የኤርትራ ሀገረ ገዥ

(6)

የነበሩት ልዑል ራስ አስራተ ካሳ በ1967 “ይህቺን ቆላ ሀገር እንደ ራስ ጸጉሬ ምድረ በዳ አደርጋታለሁ” በማለት በባርካ አውራጃ ከፍተኛ ህዝብ ያለቀበትን ዘመቻ ማካሄዳቸው በታሪክ ምሁራን ተጽፏል፡፡ በወቅቱ በኤርትራ ክፍለሀገር ወታደራዊ ኦፊሰር የነበሩት ሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ በጻፉት መጽሐፍ እንደገለጹት ከአምስት ሺህ የማያንሱ ሰላማዊ ኤርትራዊያን ራስ አስራተ ካሳ ባዘመቱት ሰራዊት ተፈጅተዋል (አጼ ኃይለ ሥላሴ በራስ አስራተ ካሳ የተወሰደውን ጭካኔ የተመላበት እርምጃ ከሰሙ በኋላ ከፍተኛ ማስጠንቀቂያ እንደሰጧቸው ይነገራል፤ በዚህም የተነሳ ራስ አስራተ በንጉሡ ላይ ቂም ይዘው ከስልጣን ሊያወርዷቸው ሲያደቡ ነበር)፡፡ ሆኖም የራስ አስራተ እርምጃ የትጥቅ አመጹን አባባሰው እንጂ አላቆመውም፡፡ በተለይ ከመንግስት ጋር ሰላማዊ ግንኙነት የነበራቸው ክርስቲያኖቹ የደጋው ኤርትራ ክፍል ነዋሪዎች በብዛት ወደ በረሃ እየወረዱ ከጀብሃ ጋር መቀላቀል የጀመሩት የራስ አስራተ ጦር በኤርትራዊያን ላይ ያደረሰው ፍጅት ከተሰማ በኋላ ነው፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የነበሩት እነ ኢሳያስ አፈወርቂ፣ ወልዳይ ግደይ፣ ሰለሞን ወልደማሪያም፣ ሙሴ ተስፋዮሐንስ ወዘተ… የመሳሰሉ ፋኖዎች ጀብሃን የተቀላቀሉት በዚያ ዓመት ነው፡፡ ከምጽዋ አካባቢም እንደ ኢብራሂም አፋ እና ረመዳን መሐመድ ኑርን የመሳሰሉ ተዋጊዎች ጀብሃን ተቀላቅለዋል፡፡

(7)

ጀብሃ “ትግሌን እንደ አልጄሪያ ነጻ አውጪዎች አጠናክርበታለሁ” ያለውን የዞን አከፋፈል በስራ ላይ አውሏል፡፡ ሆኖም በግንባሩ ውስጥ የተከሰተው ቀውስ ከቀን ወደ ቀን እየጠነከረ ነው የሄደው፡፡ ግንባሩ ኤርትራዊያንን በጎሳ እና በሀይማኖት ይከፋፍላል በማለት የተቆጡ ታጋዮችን ለማለዘብ አንዳንድ ለውጦች ቢካሄዱም ቅሬታዎቹ ሌላ መልክ እየያዙ ቀጥለዋል፡፡ ለምሳሌ በ1960ዎቹ መጨረሻ ላይ ከዩኒቨርሲቲና ከከፍተኛ ሁለተኛ ትምህርት ቤቶች ወደ ድርጅቱ የተቀላቀሉ ወጣቶች “ኤርትራን ነጻ የሚያወጣው በላብ አደር መደብ የሚመራ ሀቀኛ አብዮት ነው” የሚል መፈክር በማንሳት ግንባሩ የብሄራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት ፕሮግራም እንዲያውጅ ይወተውቱ ነበር፡፡ ይህም “ግንባሩ የማርክሲዝም ርዕዮተ ዓለም ተከታይ መሆኑን በይፋ ያሳውቅ” እንደማለት ነው፡፡ በሌላ በኩል “የድርጅቱ አመራር በጉባኤ ያልተመረጠ ስለሆነ ጉባኤ ተደርጎ አዳዲስ መሪዎች ወደ አመራሩ መምጣት አለባቸው” የሚል ጥያቄ የሚያነሱ ክፍሎች ነበሩ፡፡ በ1969 መጀመሪያ ላይ የጀብሃ አመራር ለመጀመሪያ ጊዜ ለጥያቄዎቹ አዎንታዊ ምላሽ ሰጠ፡፡ ቅሬታዎችም ሆኑ ልዩ ልዩ ጥያቄዎች በድርጅቱ ጠቅላላ ጉባኤ እንደሚመለሱ ቃል ገባ፡፡ ይሁን እንጂ በወቅቱ የሀይለ ሥላሤ መንግሥት በግንባሩ ላይ ሁለተኛ ዙር የማጥቃት ዘመቻ እያካሄደ ስለነበር ጉባኤው ከሁለት ዓመት በኋላ (1971) ሊደረግ እንደተወሰነ ለጠያቂዎቹ ተገለጸላቸው፡፡ ነገር ግን ጠያቂዎቹ በዚህ አልረኩም፡፡ “ቢያንስ አስቸኳይ ኮንፈረንስ መደረግ አለበት” በማለት ወተወቱ፡፡ የጀብሃ አመራር በዚሁ በመስማማቱ ኮንፈረንሱ በሳህል አውራጃ ውስጥ በሚገኘው “አርዳይብ”

(8)

በተባለ ቦታ ተካሄደ፡፡ በዚህ ኮንፈረንስ ላይ በውጊያ ላይ የነበሩት አንደኛና ሁለተኛ ዞኖች አልተሳተፉም፡፡ ሶስተኛ፣ አራተኛና አምስተኛ ዞኖች ብቻ ናቸው ከቦታው የተገኙት፡፡ በዚህም የተነሳ ከሶስቱ ዞኖች ወደ ጉባኤው የመጡ ታጋዮች የልባቸውን አውጥተው የሚናገሩበት ዕድል ተፈጠረ (እነዚህ ዞኖች በምስራቅና ደቡብ ኤርትራ በሚገኙ ቦታዎች የሚቀንሳቀሱ መሆናቸውን አስታውሱ፤ በጀብሃ ላይ ቅሬታ ሲያቀርቡ የነበሩትም በነዚህ ዞኖች ስር የተደራጁት ናቸው)፡፡ በኮንፈረንሱ ላይ ከደጋው የኤርትራ ክፍል ወደ ድርጅቱ የተቀላቀሉ ወጣቶች የዘመናት ብሶታቸውን ይፋ አውጥተው ተናገሩ፡፡ ለኤርትራ ነጻነት እፋለማሁ የሚለው ድርጅት የፋሺስት አዝማሚያ እየተከተለ ነው በማለት ኮነኑት፡፡ አሟሟታቸው የተደበቀ የበርካታ ታጋዮችን ስም እየጠሩ ጀብሃን አወገዙት፡፡ “ግንባሩ በአንድ ዓመት ጊዜ ራሱን ካላስተካከለ ከድርጅቱ እንወጣለን” የሚሉ መግለጫዎች ተሰሙ፡፡ የጀብሃ አመራሮች ጫናውን ለመቋቋም ከበዳቸው፡፡ “ሁሉንም እንጣራለን” በማለት ቃል ቢገቡም የተሰብሳቢዎቹን ልብ ለማግኘት አልቻሉም፡፡ በመጨረሻ ግን ሁሉም ከአመት በኋላ በሚካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ በመስማማት ተለያዩ፡፡ ከአንድ ዓመት በኋላ ደግሞ የሁሉም ዞኖች ወታደራዊ መሪዎች የተገኙበት አስቸኳይ ኮንፈረንስ “አዶብሃ” በተባለ ስፍራ ተካሄደ፡፡ በኮንፈረንሱ ላይ ዱላ-ቀረሽ ክርክር ከተደረገ በኋላ ተቀማጭነቱ በሱዳኗ ከሰላ ከተማ የሆነው “ቃኢዳ ሰውራ” (አብዮታዊ እዝ) እንዲፈርስ ተወሰነ፡፡ ከያንዳንዱ ዞን ስምንት ወጣት ሰዎች የተመረጡበትና 40 አባላት ያሉት “ቃኢዳ አል-አማ” (ጠቅላይ መምሪያ) ተመሰረተ፡፡ ሆኖም የካይሮው ላዕላይ ምክር ቤት በነበረበት ይቀጥል ተባለ፡፡ የድርጅቱ መሪዎች እርምጃውን ህገ ወጥ ቢሉትም የ“አል-አማ” አባላት ግን ህጋዊ ነን በማለት በእርምጃቸው ቀጠሉበት፡፡ ከአዶብሃ ኮንፈረንስ በኋላ በአዶብሃ ኮንፈረንስ ከተሳተፉት መካከል የሶስቱ ዞኖች (ሶስተኛ፣ አራተኛ እና አምስተኛ ዞን) ታጋዮች ልብ ለልብ ተግባቡ፡፡ ውለው ሳያድሩም “ወታደራዊ ዞን” የሚባለውን አከፋፈል ለማፍረስ ተስማሙ፡፡ “የአንዱ ዞን ታጋዮች በሌላኛው ዞን እንዳሻቸው ወታደራዊ ዘመቻ ማካሄድ ይችላሉ” በማለትም አሰመሩበት፡፡ ሊያጠቃቸው የሚመጣውን የመንግሥት ጦር ሀይል በህብረት ለመመከትም ተስማሙ፡፡ ከጥቂት ጊዜ በኋላም በነዚህ ዞኖች ውስጥ ያሉ ታጋዮች “ሰልፊ ነጻነት” እና “ህዝባዊ ኃይሊ” በሚባሉ ቡድኖች ስር ራሳቸውን አደራጁ፡፡ “ህዝባዊ ኃይሊ” በአብዛኛው የምጽዋና የሰምሃር አካባቢ ተወላጆችን ያቀፈ ነው፡፡ ቁጥራቸው አነስተኛ ቢሆንም በፖለቲካም ሆነ በወታደራዊ ችሎታ አንቱ የተሰኙ ናቸው፡፡ ረመዳን መሐመድ ኑር፣ ኢብራሂም አፋ እና መስፍን ሐጎስ የቡድኑ መሪዎች ነበሩ፡፡ የዚህ ቡድን መንቀሳቀሻ ከምጽዋ በስተሰሜን የነበረው የባህር ጠረፍ ነበር፡፡ “ሰልፊ ነጻነት” ደግሞ በአብዛኛው የሐማሴን እና የአከለ ጉዛይ ተወላጆችን ነው ያቀፈ ነው፡፡ አብርሃም ተወልደ፣ ኢሳያስ አፈወርቂ፣ ሀብተሥላሤ ገብረ

(9)

መድህን፣ ሰሎሞን ወልደማሪያም፣ ወልደ ሚካኤል ኃይለ እና ባራኺ ንጉሡ የቡድኑ መስራቾች ናቸው፡፡ ኢሳያስ አፍወርቂ የዚህ ቡድን ጊዜያዊ መሪ ሆኖ ተሰይሟል፡፡ የቡድኑ ዋነኛ መንቀሳቀሻ በደቀምሐረ ወረዳ የሚገኘው “የዓላ በረሃ” ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ቡድኖች በይፋ ከጀብሃ መገንጠላቸውን ሳያሳውቁ ትግሉን በየፊናቸው ማካሄድ ጀመሩ፡፡ ጀብሀም ስሙን በድጋሚ ላለማስጠቆር እስከ ቀጣዩ ጉባኤ ድረስ የቡድኖቹን ሁኔታ በዝምታ መከታተሉን ቀጠለ፡፡ በሌላ በኩል ጀብሃ እስከ ዛሬ ድረስ የሚጸጸትበትን ታሪካዊ ስህተት የፈጸመው በዚሁ ወቅት ነበር፡፡ ይኸውም የዑሥማን ሳልሕ ሳቤ ከስልጣን መባረር ነው፡፡ የጀብሃ መሪዎች ሳልህ ሳቤ በደገኞች ላይ የሚፈጸመውን ኢ-ፍትሐዊ ቅጣት በመቃወሙ ቂም ይዘውበታል፡፡ በተጨማሪም ከዐረቦች የሚሰጣቸው እርዳታ ወደ ኤርትራ ምድር የሚገባው በርሱ በኩል በመሆኑ በቅናት ዐይን ይመለከቱት ነበር፡፡ ስለዚህ እርሱን አባርረው ሳሊህ አህመድ ኢያይ በሚባል ሰው ለመተካት ወሰኑ፡፡ ይህንንም ሲያደርጉ በልባቸው ሳልህ ሳቤ “ሽርሽር እንጂ የበረሃ ትግል የማይችል ሰው በመሆኑ በሶሪያና ካይሮ ጎዳናዎች ተወስኖ ይቀራል” የሚል አስተሳሰብ ነበራቸው፡፡ ውጤቱ ግን እነርሱ ከጠበቁት ውጪ ነው የሆነው፡፡ ሳልህ ሳቤ በኤርትራዊያን ዘንድ ከፍተኛ ከበሬታ ያገኘበትን ገድል ለመፈጸም የተነሳሳው የጀብሀ መሪዎች ይህንን እርምጃ ከወሰዱ በኋላ ነው፡፡ ሰውዬው ጀብሃዎች እንደገመቱት በዐረብ መዲናዎች አልቀረም፡፡ በቀጥታ ወደ ሳህል በረሃ መጥቶ “ህዝባዊ ሀይሊ” ከሚባለው ቡድን ጋር ነው የተቀላቀለው፡፡ የቡድኑ ታጋዮችም ወዲያውኑ በመሪነት ቦታ ላይ አስቀመጡት፡፡ ዑስማን ሳልህ ሳቤ በተለመደው የዲፕሎማሲ ጥበቡ ከዐረብ መዲናዎች የሚያሰባስበውን የጦር መሳሪያ ወደ ኤርትራ በረሃ እያመጣ “ህዝባዊ ሀይሊ” የተባለውን ቡድን እስከ አፍንጫው ድረስ አስታጠቀው፡፡ ሆኖም ቡድኑ ከፍተኛ የሰው ሀይል እጥረት ስላነበረበት ኢሳያስ አፍወርቂ በጊዜያዊነት ከሚመራው “ሰልፊ ነጻነት” ጋር በጋራ ግንባር ለመስራት መነጋገር ጀመረ፡፡ በውይይታቸው ወደ ስምምነት ተቃረቡ፡፡ በዚህ መሀል ደግሞ ከጀብሃ ታጋዮች መካከል የማሪያ ጎሳ ተወላጆች (የአቆርዳት አካባቢ ልጆች) የሆኑት ጥቂት ሰዎች “ጀብሃ ለቤኒ አምር ልጆች ያደላል” በሚል ቂም ቋጥረው ኖሮ ከጀብሃ ተገንጥለው ወደ ሳሕል ወረዱና ከሰልፊ ነጻነት እና “ህዝባዊ ኃይሊ” ጋር የጋራ ግንባር ፈጠሩ (ይህ የማሪያ ልጆች ቡድን “ዑበል” ይሰኛል)፡፡ ጀብሃ በ1971 ድርጅታዊ ጉባኤ ጠራ፡፡ የሁለቱ ዞኖች (ዞን አንድ እና ዞን ሁለት) ተወካዮች በጉባኤው ተገኙ፡፡ ከግንባሩ የወጡት ሶስቱ ቡድኖች ግን በጉባኤው ላይ እንደማይገኙ አስታወቁ፡፡ ጀብሃ ለጊዜው እነርሱን ችላ በማለት ጉባኤውን በታቀደለት የጊዜ ሰሌዳ መሰረት አካሄደ፡፡ በጉባኤው ፍጻሜ ላይ በርካታ ስር-ነቀል እርምጃዎች ተወሰዱ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ የጀብሃ መለያ ሆኖ የሚታወቀው “ሰውራዊ ባይቶ” (“አብዮታዊ ምክር ቤት” ማለት ነው- በትግረ ቋንቋ) የሚባለው የግንባሩ ላዕላይ ምክር ቤት በዚያ ጉባኤ ውሳኔ መሰረት ተፈጠረ፡፡ እነ ህሩይ ተድላ ባይሩን የመሳሰሉ ታዋቂ ደገኛ ግለሰቦች ወደ አመራሩ መጡ (ህሩይ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ የጀብሃ ምክትል ፕሬዚዳንት ነው)፡፡ ተቀማጭነቱ ከሰላ ላይ የሆነው “አብዮታዊ እዝ” (ቃኢዳ ሰውራ) ህጋዊ ስለሆነ በዚያው ይቀጥል ተባለ፡፡ ሆኖም አላግባብ ሰው ገድለዋል የተባሉ የጦር መሪዎች ከስልጣን ተባረው በአዳዲስ ሰዎች ተተኩ፡፡ የጀብሃ መሪዎች ራሳቸውን እንዲህ ከቀያየሩ በኋላ “በድርጅቱ ውስጥ የነበረው ችግር ሙሉ በሙሉ ተፈቷል፤ ከዚህ በኋላ የሚያንገራግር ወይንም ቅሬታ አለኝ የሚል አካል ለኤርትራ ነጻነት እንቅፋት

(10)

ነው” የሚል አዋጅ አወጁ፡፡ በተጨማሪም በብዙዎች አንደበት ተደጋግሞ የሚጠቀሰውን “የኤርትራ መሬት ከአንድ ድርጅት በላይ አይችልም” የሚለውን የድርጅታቸውን መርህ በይፋ አሰሙ፡፡ በዚህም መሰረት በጉባኤው ላይ ካልተሳተፉት ሶስት ቡድኖች መካከል “ዑበል” እና “ህዝባዊ ኃይሊ” በሚባሉት ላይ ጥቃት ለመክፈት ወሰኑ፡፡ በ“ሰልፊ ነጻነት” ላይ የሚወሰደው እርምጃ ግን ለጊዜው እንዲዘገይ ተወሰነ (እንዲህ የተደረገው፣ በሁለት ምክንያት ነው ይባላል፤ አንደኛው ምክንያት “አብርሃም ተወልደ” የሚባለው የቡድኑ ዋነኛ ሰው ከጀብሃ ጋር ለመደራደር ፍላጎት እንዳለው በድብቅ መልዕክት ልኳል የሚል ነው፤ ሁለተኛውና ዋነኛው ምክንያት ደግሞ ቡድኑ በአብዛኛው ክርስትያን የሆኑ ታጋዮችን ያቀፈ በመሆኑ ከባድ እርምጃ ከተወሰደበት “ጀብሃ ጸረ-ክርስቲያን ነው” የሚለው ፕሮፓጋንዳ ይጠናከራል በማለት ስለተፈራ ነው ይባላል)፡፡

(11)

ሻዕቢያ ተወለደ ጀብሃ በአንደኛው ድርጅታዊ ጉባኤ በተወሰነው መሰረት አፈንጋጮቹን ለማጥፋት ሰራዊቱን ወደ ሳሕል በረሃ አዘመተ፡፡ የዑበል እና “ህዝባዊ ኃይሊ” አባላት በሰፈሩበት ጎራ ላይ ጥቃት ተከፈተባቸው፡፡ ሆኖም ቡድኖቹ ነቅተው ይጠብቁ ስለነበር አጥቂው ሀይል ሲመጣባቸው በሰሜን አቅጣጫ ወደ ሱዳን ሸሹ፡፡ ይህንን ያየው የጀብሃ ሰራዊት “ሰልፊ ነጻነት” የሚባለውን ቡድን ሳይነካው ወደ ባርካ ተመለሰ፡፡ “ሰልፊ ነጻነት” በበኩሉ የጀብሃን እርምጃ “እኛን ለማታለል የተደረገ ነው” በሚል ስለወሰደው ሰራዊቱን በመያዝ በፊት ወደ ነበረበት የ“ዓላ በረሃ” (አከለ ጉዛይ አውራጃ/ደቀምሐረ ወረዳ) ተመለሰ፡፡ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ከሳሕል የተባረሩት የዑበል እና “ህዝባዊ ኃይሊ” አባላት በዑስማን ሳልሕ ሳቤ መሪነት በቀይ ባህር አቋርጠው በደቡብ ኤርትራ “እምባሶይራ” በሚባለው ተራራ እንደመሸጉ ተሰማ፡፡ “የሰልፊ ነጻነት” ቡድን አባላት ከቦታው ድረስ ሄደው ከተቀበሏቸው በኋላ በፊት የተጀመረው በጋራ ግንባር የመስራት ጥያቄ በአጭር ጊዜ መልስ እንዲያገኝ ጠየቋቸው፡፡ የተቀሩት ቡድኖችም ጥያቄውን በደስታ በመቀበላቸው ቤይሩት ላይ ህብረቱ እንዲታወጅ ተወሰነ፡፡ በዚህም መሰረት በ1972 በቤይሩት ከተማ የጋራ አወጁ፡፡ ለአሰራር ያመቻል ስለተባለም “ተጋድሎ ሓርነት ኤርትራ” የሚለው የቀድሞው የድርጅታቸው ስም በነበረበት እንዲቀጥልና በስሙ ላይ “ህዝባዊ ሓርነት ኃይልታት” የሚል ቅጥያ እንዲጨመርበት ተወሰነ

(በእንግሊዝኛ Eritrean Liberation Front-Popular Liberation Forces ተብሎ ነበር

የሚጠራው)፡፡ ቡድኖቹ የግንባሩ አመራር ወደፊት እንዲመረጥም ነው የተስማሙት፡፡ “ኦሥማን ሳልሕ ሳቤ” ግን የግንባሩ የውጪ ግንኙነት ኃላፊ ሆኖ እንዲቀጥል በአንድ ድምጽ ወስነው ነበር፡፡ ይህ ግንባር በታሪክ ምዕራፎች በአጭሩ “ህዝባዊ ኃይልታት” ተብሎ ነው የታወቀው፡፡ ብዙዎች እርሱን የሚያውቁት ግን “ሻዕቢያ” በሚል የዐረብኛ ስሙ ነው (“ሻዕቢያ” ህዝባዊ ማለት ነው-በዐረብኛ፤ ነገር ግን ይህ የመጀመሪያው “ሻዕቢያ” አሁን ካለው “ሻዕቢያ” ይለያል)፡፡ “ህዝባዊ ኃይልታት” በሳሕልና በዓላ በረሃዎች እንቅስቃሴውን ሲጀምር “ጀብሃ” በከፍተኛ ሽብር ውስጥ ወደቀ፡፡ ይህ አዲስ የበቀለው ግንባር በእንጭጩ ካልተቀጨ ለስልጣኔ ያሰጋኛል በሚል ደመደመ፡፡ በተለይም የጀብሃ መሪዎች ዑስማን ሳልህ ሳቤ የግንባሩ የውጪ ግንኙነት ኃላፊ ሆኖ መሰየሙን በዝምታ ሊያልፉት አልፈለጉም፡፡ ስለዚህ የልባቸውን ለማድረስ ሰራዊታቸውን ወደ ሳሕል በረሃ አዘመቱት፡፡ ሆኖም ጀብሃዎች በአዲሱ ግንባር ተሸነፉ፡፡ እንደገና ጥቃት ቢሞክሩም አልተሳካላቸውም፡፡ ዓመቱን በሙሉ ከህዝባዊ ሀይልታት ጋር ቢዋጉም ውጤቱ ሊቀየር አልቻለም፡፡ ይባስ ብሎም በስተመጨረሻ በአዲሱ ግንባር ሙሉ በሙሉ በመሸነፋቸው ከሳሕል በረሃ ተጠራርገው ወደ ባርካ አውራጃ ገቡ፡፡ አዲሱ “ህዝባዊ ኃይልታት” ጀብሃን እንዲህ ከመከተ በኋላ ግን አንድነቱን ማስጠበቅ አልቻለም፡፡ “ዑበል” የተሰኘው ቡድን አባላት “በግንባሩ ውስጥ ተሰሚነት የለንም፤ በሌሎቹ ተውጠናል” የሚል ቅሬታ ስለተፈጠረባቸው ከአንድነት ግንባሩ በመውጣት በባርካ አውራጃ የራሳቸውን የውጊያ ግንባር

(12)

ለመክፈት ወደ ትውልድ መንደራቸው ሄዱ፡፡ ሆኖም በመንገድ ላይ ባልተጠበቀ ሁኔታ በጀብሃ ሰራዊት ቀለበት ውስጥ ገቡ፡፡ ጀብሃዎችም አንዳቸውንም ሳያስተርፉ ፈጁአቸው፡፡ በዚህም የ“ዑበል” እንቅስቃሴ ታሪክ አከተመ፡፡ በ“ህዝባዊ ኃይልታት” ውስጥ የቀሩት “ህዝባዊ ኃይሊ” እና “ሰልፊ ነጻነት” ወደ ውህደት ለመሸጋገር ከጫፍ ላይ ደረሱ፡፡ ሆኖም ሁለት ያልታሰቡ እንግዳ ክስተቶች ገፍተው ስለወጡ የውህደቱን እርምጃ ገቱት፡፡ ታዲያ እነዚህ እንግዳ ነገሮች መሰረታቸውን የጣሉት ሶስቱ ቡድኖች ከጀብሃ በይፋ ተነጥለው ከመውጣታቸው በፊት ነው፡፡ ከነዚህ ክስተቶች መካከል አንደኛው የኤርትራ ገዥ የነበሩት ልዑል ራስ አስራተ ካሳ ጀብሃን ለማጥፋት ከሰልፊ ነጻነት ጋር በስውር በተዋዋሉት መሰረት ኢሳያስ አፈወርቂን የመሳሰሉ የቡድኑ መሪዎች “ጀብሃን እስከ መጨረሻው መደምሰስ አንጂ መታረቅ አይታሰብም” የሚል አቋም ይዘው መገኘታቸው ነው፡፡ ሁለተኛው እንግዳ ክስተት ደግሞ ሲ.አይ.ኤ. በ1970 ከኢሳያስ አፍወርቂ ጋር በሚስጢር ተገናኝቶ የቀበረው ፈንጂ እየፈነዳ ማስቸገሩ ነው፡፡ የዚህ የሲ.አይ.ኤ ፈንጂ የአጭር ጊዜ ዓላማ በፍልስጥኤም ነጻ-አውጪ ድርጅት ደጋፊነት የተጠረጠረውን ጀብሃን ማዳከም ነው፡፡ የረጅም ጊዜ ዓላማው ኤርትራን አስገንጥሎ በአንድም ወቅት ከሌሎች ሀገራት ጋር በስምምነት መኖር የማትችል ሀገር ማድረግ ነው (ስለራስ አስራተ ካሳ ሴራ እና በሲ.አይ.ኤ ስለተቀበረው ፈንጂ የሴራው ተባባሪ በነበሩት አቶ ተስፋሚካኤል ጆርጆ የተጻፈውን ጽሑፍ ከዚህ በፈት አቅርቤው ነበር፡፡ ኦሪጂናሉን ዶክመንት ለማግኘት ይህንን ሊንክ ይክፈቱት http://www.ehrea.org/TesfaMikegiorgioAmarina.pdf) እነዚህ ሁለት ጎታች ድርጊቶች ሚስጢራዊ በሆነ መንገድ የተጫወቱት ሚና “ህዝባዊ ኃይልታት” ወደ አንድ ግንባር ለመለወጥ የተደረገውን ጥረት ገድለውታል፡፡ በሌላ በኩል ግን በ“ህዝባዊ ኃይልታት ኤርትራ” ውስጥ የሚገኙት አንዳንድ ስም ያላቸው መሪዎች ከጀብሃ ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለማስቆም ጥረታቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል፡፡ የአስመራ ከተማ ህዝብም “እስከ መቼ በካራ ትተራረዳላችሁ?” በማለት ሽማግሌዎችን ወደ ሁለቱም ግንባሮች መላካቸው በታሪክ ገጾች ይታወቃል፡፡ የሽማግሌዎቹ ጥረት ስለሰመረ ጀብሃ እና “ሻዕቢያ” (ህዝባዊ ኃይልታት) በ1975 የተኩስ አቁም ስምምነት አድርገዋል፡፡ ሁለት መሪዎች ደግሞ ከዚህም ይበልጥ ገፍተው ሄደው ከጀብሃ ጋር ውህደት ለመፈጸም ጥረት አድርገው ነበር፡፡ እነርሱም አብርሃም ተወልደ እና ዑስማን ሳልህ ሳቤ ነበሩ፡፡ ከሁሉ አስቀድሞ ከጀብሃ ጋር ያለው ችግር በሰላም ተፈትቶ የኤርትራ ታጋዮች ሁሉ ወደ አንድ ግንባር መምጣት አለባቸው በማለት ጥረት ያደረገው አብርሃም ተወልደ ነው፡፡ ሆኖም አብርሃም በ1971 እስከ ዛሬ ድረስ እንቆቅልሽ በሆነ መንገድ ሲሞት ጥረቱ በአጭሩ ተቀጨ (እንደሚባለው ከሆነ አብረሃም በነ ኢሳያስ አፍወርቂ ተመርዞ ነው የተገደለው)፡፡ በ1975 ግን ዑስማን ሳልሕ ሳቤ በከፍተኛ ድፍረትና ልበ ሙሉነት ከጀብሃ ጋር ወደ አንድ ግንባር የመጠቃለሉን ጉዳይ አንቀሳቀሰ፡፡ ጥረቱ ስለሰመረ ከዓመት በኋላ በካርቱም ከተማ ከጀብሃ ጋር የትብብርና የጋራ ግንባር የመፍጠር ስምምነት ተፈራረመ፡፡ ሆኖም ስምምነቱ ዘላቂ ሊሆን አልቻለም፡፡ በሀገር ቤት ያሉት እነ ኢሳያስ አፍወርቂ “ሳልህ ሳቤ የውጪ ጉዳይ ኃላፊ እንጂ የግንባሩ መሪ አይደለም” በማለት ስምምነቱን ውድቅ አድርገውበታል፡፡ በዚህም የቁርጥ ቀን ወዳጃቸው ከሆነው ሳልህ ሳቤ ጋር እስከወዲያኛው ለመቆራረጥ በቅተዋል፡፡

(13)

በነዚህ እርምጃዎች የተነሳ በጅምሩ ላይ የሶስት ቡድኖች ጥምረት የነበረው “ህዝባዊ ኃይልታት”

በስተመጨረሻ “ሰልፊ ነጻነት” በተሰኘው ቡድን ቁጥጥር ስር ገባ፡፡ ይህ ቡድን በዚሁ ስም (ህዝባዊ

ኃይልታት) ራሱን ሲጠራ ከከረመ በኋላ በ1977 የመጀመሪያ ጉባኤውን አካሄደ፡፡ በጉባኤው

በተወሰነ ውሳኔ መሰረት ስሙን ትንሽ ለወጥ ለማድረግ “ህዝባዊ ግንባር ሓርነት

ኤርትራ”/Eritrean People’s Liberation Front በሚል ተጠራ፡፡ ረመዳን መሐመድ-ኑር

ዋና ጸሐፊ ሆኖ ተመረጠ፡፡ ግንባሩን በሙሉ ሀይል የመምራት ስልጣን ግን “ምክትል ዋና ጸሓፊ” ተብሎ በተሰየመው ኢሳያስ አፍወርቂ ተጠቀለለ፡፡ የ“ብጽኣይ” እንቅስቃሴ በሻዕቢያ ውስጥ የፈነዳው የመንካዕ ንቅናቄ ከተዳፈነ በኋላ የድርጅቱ ታጋዮች ማጉረምረማቸውን አላቆሙም፡፡ በተለይ የመንካዕ መሪዎችን የገጠማቸው ሰቆቃ የተመላበት እስርና የሞት ቅጣት ብዙዎቹን አስከፍቷል፡፡ ሆኖም ታጋዩ እርስ በራሱ ይጠራጠር ስለነበር ድምጹን ከፍ አድርጎ አላሰማም፡፡ በዕድሜው ጠና ያለ አንድ ታጋይ ግን “ድርጅቱ ውስጣዊ ዲሞክራሲ እንዲኖረው አደርጋለሁ” በማለት የበኩሉን ጥረት ለማድረግ ተነሳ፡፡ ያ ታጋይ ጎይቶም በርሄ ይባላል፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የህግ ምሩቅ ነው፡፡ ሻዕቢያን የተቀላቀለው በ1972 ነው፡፡ ይህ ሰው ከፍተኛ የሆነ የስነ-ጽሑፍና የርዕዮተ ዓለም ትንታኔ ችሎታ ነበረው፡፡ በዘመኑ እጅግ በጣም ይፈለጉ የነበሩትን ማርክሳዊና የዲያሌክቲክ ፍልስፍና መጻሕፍትን ከውጪ ቋንቋዎች ወደ ትግርኛ ተርጉሟል፡፡ እርሱ ራሱ ከጻፋቸው ኦሪጂናል ጽሑፎች መካከል ደግሞ “መን እዩ ብፅአዊ? መን እዩ ሰውራዊ?” (“ጓድ” ማለት ማን ነው? አብዮታዊውስ ማን ነው?) የሚል ርዕስ ያለው ባለ 30 ገጽ መጣጥፍ ከፍተኛ ተቀባይነት እንደነበረው የታሪክ ሰዎች ይናገራሉ፡፡ ሻዕቢያ የርሱን ጽሑፎች ታጋዩን ለማስተማር ተጠቅሞባቸዋል፡፡ ይህ ሰው በዕድሜውም ሆነ በተሰጥኦው አንቱታን ያገኘ ስለሆነ ሁሉም ታጋዮች “ብጽአይ” (ጓድ) በማለት ነበር የሚጠሩት፡፡ “ብጽአይ” ጎይቶም በመንካዕ ንቅናቄ ውስጥ ቀጥተኛ ተሳትፎ አላደረገም፡፡ ሆኖም ውጥረቱን እንዲሸመግሉ ከተመረጡ ሽማግሌዎች መካከል አንዱ ነበር፡፡ እነ ኢሳያስ የመንካዕ መሪዎችን በከባድ ቅጣት ዝም ሲያሰኟቸው ግን “የተሰጠው ፍርድ ኢ-ፍትሓዊ ነው” በሚል ተቃውሞ አሰምቷል፡፡ በዚህም ከሃላፊነት እንዲወርድ ተደርጓል፡፡ ታዲያ ብፅአይ ጎይቶም ስልጣኔን ተቀማሁ ብሎ ወደ

(14)

ኩርፊያ አልሄደም፡፡ ድምጹን አጥፍቶ በድርጅቱ ውስጥ ዲሞክራሲ የሚሰፍነበትን መንገድ ያውጠነጥን ነበር፡፡ በ1975 መጨረሻ ላይም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የነበሩ ጥቂት ጓዶች ግንባሩን ሲቀላቀሉ ከነርሱ ጋር መቀራረብ ጀመረ፡፡ ከተማሪዎቹ ጋር ባደረገው ውይይትም “ድርጅቱን ዲሞክራሲያዊ ማድረግ አለብን” የሚል አጀንዳ አስታጠቃቸው፡፡ እነዚያ ወጣቶችም የርሱን ሀሳብ ማቀንቀን ጀመሩ፡፡ በዚህ ነጥብ ዙሪያ ታጋዩን ማወያየትና ድጋፍ ማሰባሰብ ሞከሩ፡፡ አንዳንዶች ወደነርሱ ተጠጉ፡፡ ብዙዎቹ ግን የመንካዕ ትውስታ ከአዕምሮአቸው ያልጠፋ በመሆኑ ወደ ብጽአይ ጎይቶምና ጓዶቹ ለመጠጋት አልፈቀዱም፡፡ እነ ብጽአይ ግን ጥረታቸውን ቀጠሉ፡፡ በርካታ የቀድሞ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ድጋፍ ሰጡአቸው፡፡ ሆኖም ዓላማቸውን በሚያስፈጽሙበት መንገድ ላይ በመምከር ላይ ሳለ ግን በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡ የስለላ መረቡን በሁሉም የሻዕቢያ ታጋዮች ላይ እንደ ሸረሪት ድር ያደራው የ“ሀላዋ ሰውራ” አዳኞች በቀላሉ “ቀጨም” አደረጓቸው፡፡ የንቅናቄው መሪዎችና ተባባሪዎች የተባሉት በሙሉ እየተፈለጉ ታሰሩ፡፡ የ“ሀለዋ ሰውራ” ኃላፊዎች ብጽአይ ጎይቶምንና ጓዶቹን ለአራት ዓመታት በእስር ካቆዩአቸው በኋላ በ1980 በሞት ቀጡአቸው፡፡ ብጽአይ ጎይቶም የተረጎማቸው መጻሕፍትና በራሪ ወረቀቶችም ከያሉበት እየተሰበሰቡ ተቃጠሉ፡፡ በጎይቶም ጽሑፎች የተበላሸውን የታጋይ አዕምሮ ለማደስ በሚልም ስታሊናዊ የሶሻሊዝም ፍልስፍና ድርሰቶች በብዛት እንዲተረጎሙ ተደረጉ (የትርጉም ስራውን በዋናነት ያከናወነው በ1985 ገደማ በኢትዮጵያ የኤርትራ አምባሳደር የነበረውና አሁን በሱዳን የተባበሩት መንግሥታት ልዩ መልዕክተኛ ሆኖ የሚያገለግለው ሀይሌ መንቆርዮስ እንደሆነ ይነገራል)፡፡ ይህ ብዙ ሳይራመድ በእንጭጩ የተቀጨው ንቅናቄ “ብፅአይ ምንቕስቓስ” ይባላል፡፡ “የጓዱ እንቅስቃሴ” ማለት ነው፡፡ “ጓድ” ወይንም “ብፅአይ” ተብሎ የሚጠራው ጎይቶም በርሄ ነው፡፡ ከርሱ ጋር በቅርበት ሆኖ እንቅስቃሴውን መርቷል የሚባለው ደግሞ ዓለም አብርሃ የተባለ ታጋይ ነው፡፡ እነዚህ ጓዶች እንደ “መንካዕ” ንቅናቄ መሪዎች “የድርጅቱ አመራር ከስልጣን ይውረድልን” አላሉም፡፡ በድርጅቱ ውስጥ ዲሞክራሲ እንዲሰፍን ለመጠየቅ ብቻ ነበር የተነሱት፡፡ ሆኖም የሰልፊ ነጻነት መሪዎች በእንቅስቃሴው አልተደሰቱም፡፡ እንዲያውም የድርጅቱን ህልውና የሚያናጋ መናፍቃዊ ንቅናቄ አድርገው ነው የወሰዱት፡፡ ሻዕቢያዎች “የብፅአይ ምንቕስቃስ” መሪዎች “የኤርትራ አብዮታዊ ፓርቲ (ERP) የተባለ ህገ-ወጥ ፓርቲ በግንባሩ ውስጥ አቋቁመዋል፤ የታወቀውን የግንባሩን ሶቪየት ቀመስ የርዕዮተ ዓለም አቅጣጫ በመቀልበስ የሊቀመንበር ማኦ ዜዱንግን መስመር ለማስፈን ሞክረዋል፤ በመሆኑም የሞት ቅጣት መፈጸሙ በግንባሩ ህግ መሰረት ተገቢ ነው” ይላሉ፡፡ ሆኖም ይህ “የኤርትራ አብዮታዊ ፓርቲ” የተሰኘ ፓርቲ በግንባሩ ውስጥ ስለመፈጠሩ ለማረጋገጥ አልተቻለም፡፡ በዚህ ንቅናቄ ጦስ ታስረው ህይወታቸው ካለፈው ታጋዮች መካከል ጎይቶም በርሄ (“ብፅአይ”)፣ ዓለም አብረሃ፣ መሲህ ርዕሶም፣ ተክላይ ገብረ ክርስቶስ፣ ሚካኤል በረከተአብ፣ ሀይሌ ዮሐንሶም፣ ሳሙኤል ገብረ ድንግል፣ በረከት ሀይሌ፣ ሀይሌ ሀብተጽዮን እና ሌሎችም ይገኙባቸዋል፡፡ ተወልደ እዮብ የሚባለው የቀድሞው የድርጅቱ ቁልፍ ሰውም ከነዚህ ሴረኞች ጋር አብረሃል በሚል በጥይት ተደብድቦ ተረሽኗል (እነዚህ ታጋዮች የተረሸኑት በ1980 ሳሕል በረሃ ውስጥ በሚገኘው አራግ በተሰኘ ቀበሌ ነው)፡፡ === የ“የማናዊ” (ቀኝ መንገደኞች) እንቅስቃሴ====

(15)

ይህኛው እንቅስቃሴ የብጽዓይ ንቅናቄ ተከታይ ሆኖ ነው የፈነዳው፡፡ ንቅናቄው የተካሄደው “ሰልፊ ነጻነት” እና “ህዝባዊ” ሀይሊ በይፋ ተዋህደው “ህዝባዊ ግንባር ሓርነት ኤርትራ” የተሰኘውን ግንባር መፍጠራቸው ከተነገረበት ጊዜ ትንሽ ቀደም ብሎ ነው (በተጨማሪም በዚያ በወቅት (1977-78) ብዙዎቹ የኤርትራ ከተሞች ከመንግሥት እጅ በመውጣት በሻዕቢያ እና ጀብሃ ቁጥጥር ስር ገብተው ነበር)፡፡ በዚህ ንቅናቄ ገፍቶ የወጣው ዋነኛ ጥያቄ “በግንባሩ ውስጥ እየተስፋፋ የመጣው ሙስናና ብልሹ አሰራር ይወገድ” የሚል ነው፡፡ ይሁንና የዚህ ንቅናቄ ጀማሪ ማን እንደሆነ በትክክል አይታወቅም፡፡ በንቅናቄው ውስጥ ከተሳተፉት ግንባር ቀደም መሪዎች መካከል ዶ/ር እዮብ ገብረ-ልዑል፣ መሓሪ ግርማ-ጽዮን፣ ገብረ-ሚካኤል መሐሪ-እዝጊ፣ ህብረት ተስፋ-ጋብር፣ ኪዳኔ አቤቶ፣ ፍሥሐዬ ኪዳኔ፣ አርአያ ሰመረ፣ አማኑኤል ፊላንሳ የተባሉት ይጠቀሳሉ (ብዙዎቹ በአውሮጳ ሀገራት የተማሩ ናቸው)፡፡ የሻዕቢያ መሪዎች በንቅናቄው የተሳተፉ ታጋዮችን “የቀይ መንገደኛነት ፈለግ ተከታዮች” በማለት ይጠሯቸዋል፡፡ እነዚያ የንቅናቄ መሪዎች ጥያቄዎቻቸውን ለሻዕቢያ አመራር ባቀረቡ ማግስት ነው የታሰሩት፡፡ ታዲያ ንቅናቄው ከተዳፈነና ሻዕቢያ አንደኛ ድርጅታዊ ጉባኤውን ካካሄደ በኋላ የቀድሞ የግንባሩ ቀንደኛ መሪ እና የሀለዋ ሰውራ ዋና ጸሓፊ የነበረው ሰለሞን ወልደማሪያምም ከንቅናቄው ጋር ንክኪ አለው ተብሎ በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡ የግንባሩ ዋነኛ መርማሪ የነበረው ሀይሌ ጀብሃም በዚያው ወቅት እንዲታሰር ተደርጓል፡፡ ሀይሌ ጀብሃ የታሰረው “በእስረኞች ላይ ከመጠኑ ያለፈ ኢ-ሰብአዊ ሰቆቃ ይፈጽማል” በሚል ምክንያት ነው፡፡ በርግጥም በርካታ ኤርትራዊያን ስለርሱ ጭካኔና ገዳይነት በሰፊው ጽፈዋል፡፡ ለምሳሌ እውቁ ኤርትራዊ ምሁር ዶ/ር በረከት ሀብተስላሴ በቅርቡ ከአንድ ድረ-ገጽ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ሀይሌ ጀብሃ አንዱን እስረኛ በብትር ጭንቅላቱን እየቀጠቀጠ ሲመረምረው ማየታቸውን መስክረዋል፡፡ ሰለሞን ወልደማሪያም የታሰረበት ምክንያት ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ሰለሞን ወልደማሪያም በግንባሩ ውስጥ የነበረው ተፈላጊነት እየቀነሰ መምጣቱን የሚያሳዩ ምልክቶች የታዩት ቀደም ብለው ነው፡፡ ለምሳሌ በ1975 መጨረሻ ላይ ለህክምና ፖርት ሱዳን ደርሶ ከተመለሰ በኋላ ቁልፍ ከሆኑ የድርጅቱ የስልጣን ቦታዎች ተገፍቶ የካድሬ ትምህርት ቤት አሰልጣኝ እንዲሆን ተመድቧል፡፡ የሀለዋ ሰውራ ዋና ጸሓፊነቱንም ከህዝባዊ ሀይሊ ለመጣው ዓሊ ሰዒድ አብደላ አስረክቧል፡፡ እርሱ ግን የድርጅቱ ጉባኤ እስኪካሄድ ድረስ የግንባሩ መሪዎች ይከዱኛል የሚል ጥርጣሬ አልነበረውም፡፡ ለሰለሞን ሁሉም ነገር ፍንትው ብሎ የታየው 37 አባላት ያሉት የማዕከላዊ ኮሚቴ ምርጫ በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡ በዚያ ምርጫ ላይ ሰለሞን በእጩነት ሲጠቆም ካድሬው በከፍተኛ ጩኸት ተቃውሞውን እንደገለጸ ይወሳል፡፡ አንዳንድ ካድሬዎች ከመቀመጫቸው እየተነሱ “ይህ ሰው የቀኝ መንገደኞቹ አንጃ መሪ ነው፤ ለርሱ እስር ቤት እንጂ ስልጣን አይገባውም” የሚል ሐሳብ መስጠታቸው ተመዝግቧል፡፡ በዚህም ሳቢያ ከኢሳያስ አፈወርቂ በፊት ወደ ዓላ በረሃ ሄዶ ከጥቂት ወጣቶች ጋር “ሰልፊ ነጻነት” የተባለውን ቡድን የመሰረተው ሰለሞን ወልደማሪያም “አዛዥ ናዛዥ” ሆኖ ብዙዎችን ካንቀጠቀጠበት መንበረ ስልጣን ላይ ተገፍትሮ ወደታች ተወርውሯል፡፡ ኢሳያስ አፈወርቂ ሰለሞንን ከስልጣኑ ያስነሳው “ይህ ወጣት በድርጅቱ ውስጥ ቁልፍ የሆኑ ቦታዎችን በመዳፉ ጠቅልሎ በመያዙ ወደፊት ከሊቀመንበርነቴ ያባረኛል” የሚል ስጋት ስለገባው መሆኑን ታሪኩን የሚያውቁ ምስክሮች ያስረዳሉ፡፡ በርግጥም ሰለሞን በሰልፊ ነጻነት ውስጥ ፈላጭ ቆራጭ

(16)

ሰው ነበር፡፡ ኢሳያስ አፈወርቂ የቡድኑ መሪ ሆኖ ቢቀመጥም ድርጅቱን በቀጥታ የሚመራው ሰለሞን ወልደማሪያም ነበር፡፡ በወቅቱ የድርጅቱ አባል የነበሩት አቶ አድሓኖም ፍትዊ የተባሉ ኤርትራዊ በጊዜው የነበረውን የስልጣን ክፍፍል ሲያስረዱ “ሰለሞን ሁሉንም ነገር ነበር፤ የሀለዋ ሰውራ ዋና ጸሐፊ ነው፡፡ ወታደራዊ አዛዥም ነው፤ የስልጠና ማዕከል ሀላፊም ነው፤ የጠቅላይ እዙ የበላይ አዛዥም ነበር፤ በግንባር ያለውን ጦር የሚያንቀሳቅሰው እርሱ ነው፡፡ ኢሳያስ አፈወርቂ ለስም ብቻ ነው ሊቀመንበር ሆኖ የተቀመጠው” በማለት አስረድተዋል፡፡ ታዲያ ኢሳያስ ሰለሞንን ከስልጣን ያስነሳው ብልጠት በተመላበት ዘዴ ነው፡፡ ሰለሞን ለረጅም ጊዜ የጉበት በሽተኛ እንደሆነ ስለሚታወቅ “እስከዛሬ ድረስ ለኛ ስትል ደክመሃል፤ አሁን ግን መታከም አለብህ፤ ህክምና እያለ መሞት የለብህም፤ ሱዳን ሄደህ ከፍተኛ ሐኪም መጎብኘት አለብህ” አለው፡፡ በተጨማሪም “ኡሥማን ሳልህ ሳቤ የድርጅታችንን የእርዳታ መስመር ስለዘጋብን ወደ ውጪ ሄደህ እርሱንም ማስከፈት አለብህ፤ ይህንን ማድረግ የምትችለው አንተ ብቻ ነህ” በማለት አከለበት፡፡ ሰለሞን የኢሳያስን ምክር ሲሰማ በልቡ ኩራት ተሰማው፡፡ “ለካስ እንዲህ ዓይነት ትልቅና ተፈላጊ ሰው ኑሬአለሁ?” በማለት ተንጠራራ፡፡ ወዲያኑ ስልጣኑን በሙሉ ለኢሳያስና ለተከታዮቹ አስረክቦ ወደ ፖርት ሱዳን ሄደ፡፡ እነ ኢሳያስም የርሱን እግር ተከትለው በድርጅቱ ቁልፍ ቦታዎች ላይ ሰዎቻቸውን አስቀመጡ፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ የሰለሞንን ግለኝነትና የስልጣን ጥመኛነት የሚያስረዳ ፕሮፓጋንዳ በሰፊው ተናፈሰ፡፡ ታዲያ ታጋዩም ሰለሞንን በፊቱኑ ይጠላው ነበርና ፕሮፓጋንዳውን ሲሰማ “ይህ አምባገነን! እርሱ ነው ለካስ ሁሉንም ሲቆላልፍ የነበረው” በማለት ተራገመ፡፡ ሰለሞን ህክምናውን ጨርሶ ከሱዳን መጣ፡፡ እነ ኢሳያስ ስልጣኔን ያስረክቡኛል ብሎ ሲጠብቅ “ላንተ እረፍት ስለሚያስፈልግህ የድርጅቱ ጉባኤ እስኪካሄድ ድረስ ቀለል ባለው የካድሬ ስልጠና ስራ ላይ መድበንሃል” አሉት፡፡ ሰለሞንም ምንም ሳይጠራጠር በስልጠና ስራ ላይ ተሰማራ፡፡ የድርጅቱ ጉባኤ ተካሂዶ በድርጅታዊ መንገድ በተካሄደው ምርጫ ከአመራሩ ሲወገድ ግን ከእንቅልፉ ባነነ፡፡ “የገዛ ወዳጆቼ ተጫወቱብኝ እያለ” ተቆጨ፡፡ ከዚያ በኋላ ነገረ-ስራው ሁሉ የግንባሩን መሪዎች በአደባባይ መሄስና ማብጠልጠል ሆነ፡፡ እርሱ ራሱ ያጠፋቸውንም ጥፋቶች በግልጽ ማውገዝ ጀመረ፡፡ በተለይ በከረን ከተማ በተደረገ ታላቅ ህዝባዊ ስብሰባ ላይ ስለ መንካዕ ንቅናቄ መሪዎች ሲጠየቅ “የተሰጠው ፍርድ ትክክል አይደለም፤ የህዝብ ልጆችን ገድለን ቀብረናል” የሚል ምላሽ ሰጠ፡፡ ታዲያ እርሱ በየወረዳው እየሄደ የሚናገረው ንግግር ወደነ ኢሳያስ ይደርስ ሰለነበር መላ እንዲበጅለት ተወሰነ፡፡ ካድሬዎች በድርጅቱ ጉባኤ ላይ ያነሱትን ክስ እንደ አዲስ በማንቀሳቀስ “የየማናዊ ምንቓስቓስ ደጋፊ ነህ” ተብሎ ታሰረ፡፡ ለአራት ዓመታት በሀለዋ ሰውራ ከቆየ በኋላ በ1983 ሳህል ውስጥ ሀክሺብ በተባለ ስፍራ ተረሸነ፡፡ በሰለሞን ወልደማሪያም ላይ የተላለፈው የሞት ፍርድ አይበዛበትም፡፡ ይህ ፍርድ እርሱ ራሱ በ“ሀለዋ ሰውራ” ሲፈጽመው ከነበረው ምህረት የለሽ ሰቆቃ እና ርሸና ጋር ሲነጻጸር እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ ችግሩ ግን ፍርዱ በስነ-አመክኖአዊ መንገድ ያልመጣ መሆኑ ነው፡፡ የሻዕቢያ ሰዎች ሰለሞንን የረሸኑት በኢሳያስ አፈወርቂ ስልጣን ላይ አደጋ የደቀነ ሆኖ በመገኘቱ ብቻ ነው፡፡ በተጨማሪም ሰለሞን ከስልጣን ከተወገደ በኋላ በሄደባቸው ቦታዎች ባይለፈልፍ እና ታማኝ መስሎ ስራውን ቢቀጥል ኖሮ ሻዕቢያዎች “ከስልጣን ተወግዶ እንኳ ሞራሉ ያልተነካ፤ ለስልጣን

(17)

የማይስገበገብ ትክክለኛው የህዝብ ልጅ” በማለት በአንድ ቦታ ላይ ይሸጉጡት እንደነበር አያጠራጥርም፡፡ ይሁንና ሰለሞን እንደ ጓዶቹ ብልህ ሆኖ አልተገኘም፡፡ እዚያው “ሀለዋ ሰውራ” ውስጥ ተደራራቢ ስቃይ አይቶ፣ በቅማልና በትኋን ከተበላ በኋላ የመቀበሪያ ጉድጓዱን ራሱ ቆፍሮ በጥይት ተሰናብቷል (በየማናዊ ንቅናቄ ሰበብ የተያዙ ታጋዮች ከርሱ ቀደም ብለው በ1980 ነው የተረሸኑት፡፡ ሀይሌ ጀብሃም ከነርሱ ጋር ነበር የተገደለው)፡፡ በእስከ አሁኑ ትረካዬ እንዳያችሁት “ሀለዋ ሰውራ” የሚል ስም ደጋግሜአለሁ፡፡ በዚህ ስም የሚጠራው በሻዕቢያ ውስጥ እጅግ የሚፈራ ተቋም ነው፡፡ ለመሆኑ ይህ ብዙ ያልተጻፈለት ተቋም ምን ይመስላል? ወደፊት እናየዋለን፡፡ በዚህ ክፍል አስቀድሜ ቃል በገባሁት መሰረት ስለ አንድ የሻዕቢያ ተቋም በመጠኑ እናወጋለን፡፡ ሀለዋ ሰውራ “ሀለዋ ሰውራ” የተሰኘ ስም ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት በበዓሉ ግርማ “ኦሮማይ” ውስጥ ነው፡፡ የኦሮማዩ “ስዕላይ በራኺ” የሀለዋ ሰውራ ዋና ጸሓፊ ነው በሚል በድርሰቱ ውስጥ ተጠቅሷል፡፡ ነገሩ ግን ልብ ወለድ ነው፡፡ ስዕላይ በተሰኘ ስም የተጠቀሰው ገጸ-ባህሪ የሀለዋ ሰውራ ዋና ጸሃፊ ሆኖ አያውቅም፡፡ ሆኖም የእስር ቤቱ ሃላፊ ነበር፡፡ ታዲያ ስለሻዕቢያ ሀለዋ ሰውራ የሚያውቀውን ሚስጢር ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ለህዝብ የገለጸው ይኸው በበዓሉ ብዕር “ስዕላይ በራኺ” ተብሎ የተጠራው ሰው ነው፡፡ የዚህ ሰው ትክክለኛ ስም ተክላይ ገብረማሪያም ነው፡፡ በሻዕቢያ ውስጥ ይበልጥ የሚታወቀው ግን “ተክላይ አደን” በተሰኘው የበረሃ ስም ነው፡፡ ተክላይ የሻዕቢያ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ነበር፡፡ በ1981 (እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1973) ከሻዕቢያ ከድቶ ለደርጎች እጁን ከሰጠ በኋላ ከኢትዮጵያ ሬድዮ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ “ሀለዋ ሰውራ” ስለሚባለው የሻዕቢያ ሚስጢራዊ ተቋም የሚያውቀውን ሁሉ ዘርዝሯል፡፡ ሌሎችም እንደዚሁ ስለ “ሀለዋ ሰውራ” የሚያውቁትን ተናግረዋል፡፡ በዚህ ጽሑፍ የተዘረዘረው መረጃ የተገኘው ግን ከልዩ ልዩ የኤርትራ ድረ-ገጾች፣ ከመጽሔቶችና ከጋዜጦች ነው፡፡ በነገራችን ላይ ተክላይ በ“ኦሮማይ” ውስጥ የተጠቀሰውን የሻዕቢያ ስውር አርበኛነት ሚና አልተጫወተም፡፡ በዓሉ “ኦሮማይ” ብሎ የገለጸው አደገኛ ተልዕኮ ልብ ወለድ ነው፡፡ እውነተኛው ተክላይ አደን በደርግ መንግሥት ዘመን በልዩ ልዩ ቢሮዎች ሲሰራ ከሰነበተ በኋላ ደርግ ሲወድቅ ወደ ኔዘርላንድ ሸሽቷል፡፡ የዛሬ አስር ዓመት ገደማም በስደት ባለበት ሀገር ህይወቱ አልፏል፡፡ ***** የኤርትራ ሰዎች “ሀለዋ ሰውራ” የሚባለውን ተቋም Gestapo ከሚባለው የናዚ ጀርመኖች የስለላና የአፈና ድርጅት ጋር ያመሳስሉታል፡፡ ሆኖም “ሀለዋ ሰውራ”ን በዚያ ደረጃ ለመፈረጅ ያዳግታል፡፡ ቢያንስ ጉልበቱና አቅሙ ከዚያ ያንሳሉ፡፡ ይሁንና በሀለዋ ሰውራም በርካታ ሰዎች መሰቃየታቸውን ይናገራሉ፡፡ “ሀለዋ ሰውራ” በቀጥታ ሲተረጎም “አብዮት ጥበቃ” ማለት ነው፡፡ በዚህ ስም የሚጠራው የሻዕቢያ የስለላና የምርመራ ጠቅላይ መምሪያ በስሩ ሶስት ክፍሎች አሉት፡፡

(18)

1. የመረጃ ክፍል፡- ማንኛውም የሻዕቢያ አባል አመራሩን የሚቃወም ንግግር ሲናገር እና ጽሑፍ ሲያሰራጭ ቢገኝ ሪፖርት የሚያደርገው ይህ ክፍል ነው፡፡ እንደሚባለው በትግሉ ዘመን ሻዕቢያ በሺህ የሚቆጠሩ ሰላዮችን በታጋዮቹ መካከል አሰማርቶ ነበር፡፡ እነዚያ ሰላዮች ከታጋዩ የቃረሙትን ወሬ ወደ ዋና ክፍሉ ሪፖርት ያደርጋሉ፡፡ ታዲያ ሻዕቢያ የመንካዕ እና የብፅአይ ንቅናቄዎች ከመከሰታቸውም በፊት አባላቱን እርስ በራስ እንዲጠራጠሩ አድርጎ አቆላልፎአቸው እንደነበር ይነገራል፡፡ አንድ ታጋይ ዕድሜው እንዲረዝም ከፈለገ አመራሩን ማሞገስ ወይንም ዝም ማለት ይገባዋል፡፡ 2. የምርመራ ክፍል፡- በሀለዋ ሰውራ ሰላዮች ተጠቁሞ የተያዘ ሰው ወደዚህ ክፍል ይተላለፋል፡፡ ይህ ክፍል ጥፋት ተገኝቶባቸዋል ተብለው የተያዙ ተጠርጣሪዎች ሚስጢር እንዲያወጡ በማለት በልዩ ልዩ የምርመራ ቴክኒኮች ይጠቀማል፡፡ ዋነኛው ስልት ግን ተጠርጣሪዎችን መግረፍና ማሰቃየት ነው፡፡ 3. የእስረኛ ክፍል፡ እስረኞች በምርመራ ላይ እያሉ የሚቆዩበት ክፍል ነው፡፡ በምርመራው ጥፋተኛ ተብለው ፍርድ የተላለፈባቸው ተጠርጣሪዎችም የሚታሰሩት በዚሁ ክፍል ነው፡፡ ታዲያ ታሳሪዎቹ በሰላም አይቆዩም፡፡ በየጊዜው ሰቆቃና ስቃይ ይፈጸምባቸዋል፡፡ ከሻዕቢያ እስር ቤት በህይወቱ የወጣ ሰው ዕድለኛ ነው-ታዛቢዎች እንደሚሉት፡፡ በትግሉ ዘመን ከ3000 በላይ የሚሆኑ ሰዎች በሀለዋ ሰውራ እስር ቤቶች ተሰቃይተው እንደሞቱ የኤርትራ የሰብዓዊ መብት ቡድኖች በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ ይፋ አድርገዋል፡፡ ሻዕቢያ በትግል ዘመኑ አምስት ያህል እስር ቤቶች የነበሩት ሲሆን ሁሉም የሚገኙት በሳህል አውራጃ ነው፡፡ ከነዚህ እስር ቤቶች መካከል አራግ እና ሀክሺብ በተባለ ቦታ የሚገኙት ከፍተኛ የስቃይ ቦታዎች እንደሆኑ ይነገራል፡፡ በሻዕቢያ እስር ቤቶች ስለሚፈጸመው ሰቆቃና ስቃይ ብዙ ተብሏል፡፡ ምግብና ውሃ መከልከል፣ እስረኞች ለተከታታይ ቀናት እንዳይተኙ መከልከል፣ እስረኞች ለረጅም ጊዜ ብርድ ላይ እንዲቆሙ ማድረግ፣ ለረጅም ጊዜ በአንድ ጎን ብቻ እንዲተኙ ማድረግ፣ ሽንት እንዳይሸኑ መከልከል፤ እስረኛው በአፉ አንድም ቃል እንዳይናገር መከልከል የመሳሰሉት የመጀመሪያ ደረጃ የማሰቃያ ስልቶች ሊባሉ ይችላሉ፡፡ እስር ቤቱ በቅማልና በትኋን የተወረረ ስለሆነ እስረኛው በነርሱ ሲሰቃይ ነው የሚከርመው፡፡ እስረኛው ለምርመራ የሚወሰደው ከእኩለ ሌሊት በኋላ ነው (ቀን ላይ ሌሎች ታጋዮች እንዳያዩት ተብሎ ነው እንዲህ የሚደረገው)፡፡ ይህ የምርመራ እጣ የወደቀበት እስረኛ መፈጠሩን እስኪጠላ ድረስ ይገረፋል፡፡ አለፍ ሲልም በሳንጃ የሚወጋ አለ፡፡ ቆሻሻ ውሃ በተጠራቀመበት በርሜል ውስጥ ፊቱን መክተት፣ ገላን በእሳትና በፈላ ዘይት ማቃጠል፣ የእስረኛውን ጸጉር ማቃጠልና ሌሎችም ስቃዮች ይወርዱበታል፡፡ በስቃዩ ተጸጽቶ ሚስጢር ያጋለጠ፣ ወይንም ጥፋተኛ ነኝ ብሎ ግለ-ሂስ ያወረደ ሰው ህይወቱ ሊተርፍ ይችላል፡፡ ምንም ሚስጢር ያልተናገረ ግን ሞት ነው የሚጠብቀው፡፡ ታዲያ በራሱ አባላት ላይ እንዲህ የሚጨክነው ሻዕቢያ የጦር ምርኮኞችን ብዙም አይወጥራቸውም፡፡ በምርኮኞች ላይ የሚካሄደው ግርፊያ እና ድብደባ በመጠኑ አነስ ይላል፡፡ በተለይ ምርኮኞቹ ማዕረግ ያላቸው ከሆነ በጣም ይንከባከባቸውና ሊጠቀምባቸው ይሞክራል፡፡ ስለደርግ መንግሥት የሚያውቁትን ወታደራዊ መረጃ እንዲሰጡት ስሜታቸውን ይኮረኩራል፡፡ ሆኖም ሁሉም ምርኮኛ እና እስረኛ በጉልበት ስራ እንዲሳተፍ ይገደዳል፡፡ በተለይ የናቅፋ ተራሮችን እያቆራረጡ ወደ ሰሜን

References

Related documents

In general, human capital strategy including training, development, and empowerment is formulated in universities of medical sciences throughout the country and

In the current trends of optimizing machining process parameters, various evolutionary or meta-heuristic techniques such as Particle Swarm Optimization (PSO), Genetic Algorithm

We nd that if individuals dier in initial wealth and if commodity taxes can be evaded at a uniform cost, preferences have to be weakly separable between consumption and labor

The table contains data for all EU-27 countries on temporary employment (in thousands) for NACE sectors L, M and N (rev 1.) and O, P and Q (rev.. Data are presented separately

Aboriginal and Torres Strait Islander absolute cardiovascular risk assessment and management: systematic review of evidence to inform national guidelines.. Public Health

Variables observed were the chemical compositions i.e dry matter (DM), organic matter (OM), crude protein (CP), ether extract (EE), crude fiber (CF), nitrogen free extract

Development of the curriculum of the Master of Advanced Industrial Management European Academy on Industrial Management (AIM) Industrial enterprises & Organizations.

It is the (education that will empower biology graduates for the application of biology knowledge and skills acquired in solving the problem of unemployment for oneself and others